Thursday, September 26, 2013

አዲስ አበባ ሆይ ድምጽሽን አሰሚ ! በአማኑኤል ዘሰላም

አዲስ አበባ ሆይ ድምጽሽን አሰሚ !
አማኑኤል ዘሰላም
amanuelzeselam@gmail.com
መስከረም 15 ቀን 2006 ዓ.ም

በደሴ፣ ጎንደር፣ ባህር ዳር፣ ፍቼ፣ አዳማ/ናዝሬት፣ ሮቢ/ባሌ፣ መቀሌ፣ ወላይታ ሶዳ፣ ጂንካ፣ አርባ ምንጭ …ሰላማዊ ሰልፎችና ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች ተደርገዋል። በአዋሳ፣ ድሬደዋ፣ ወሊሶ፣ አሶሳና ጋምቤላ፣ እቅዱ ዉስጥ የነበሩም ቢሆንም በገንዘብ አቅም ምክንያት ለጊዜዉ ሰልፎች ሊካሄዱ  አልቻሉም።
መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም ትኩረቱ አዲስ አበባ ፊንፊኔ ይሆናል። የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት የጀመረዉ የመጀመሪያዉ  ዙር የሶስት ወራት እንቅስቃሴ የሚደመደምበት !
ከአዲስ አበባው ሰልፍ ጋር በተገናኘ፣ የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት  እና የአሁኑ የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶር ነጋሶ ጊዳዳ  በፖሊሶች መታሰራቸዉን የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት በፌስቡኩ  ዘግቧል።
«ፖሊስ የቀድሞውን የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት አሰረ። የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ፕሬዘዳንት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ የታሰሩ የፓርቲውን የቅስቀሳ ቡድን አባላት ለማስፈታት ወደ ጉለሌ ክፍለ ከተማ የሽሮ ሜዳ ፖሊስ ማዘዣ ጣብያ በማምራት ለፖሊሶቹ «ልጆቹ የፈጸሙት ህገ ወጥ ድርጊት የለም፣ ሲቀሰቅሱ የነበሩትም እውቅና የተሰጠውን ሰላማዊ ሰልፍ ነው፡፡ ቅስቀሳው ህገ ወጥ ነው የምትሉም ከሆነ እነርሱን የላኳቸው እኔ በመሆኔ እኔን ልታስሩኝ ትችላላችሁ » ብለዋል፡፡
ፖሊስ የቀድሞውን የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳን በማሰር ወጣቶቹን ለቅቋቸዋል»
የኢሕአዴግ ፓርቲ በአንድ በኩል እየፈቀደ፣ በሌላ በኩል የፈቀደዉን የሚሽር ተግባራት መፈጸሙ ብዙዎቻችንን  እያስገረመ ነዉ። ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ  የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ፍላጎት እንዳላቸው የሚናገሩ ጥቂቶች አይደሉም። የዉጭ ጉዳይ ሚኒስተሩም ዶር ቴዎድሮስ አዳኖም፣  ድርጅታቸው ኢሕአዴግ ለዴሞክራሲ ግንባታ ቁርጠኝነት እንዳለው ገልጸውም ነበር። ለዚህም ሳይሆን አይቀርም፣ ሰላማዊ ሰልፎች የማድረግ፣ እስረኞችን ያለገደብ የመጠየቅ ፣ የፖለቲካ ክርክሮችን በኢቲቪ የማድረግ የመሳሰሉትን፣  በመለስ ዜናዊ ዘመን ከነበረዉ ሁኔታ ጋር ሲነጻጸር፣ የተሻሉ ሁኔታዎችን ማየት የጀመርነዉ።
ነገር ግን፣  በጎን፣  የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያምን ዉሳኔ ለማክሸፍ፣ ጠቅላይ ሚኒስተሩ  በሕዝብ እንዲጠሉ፣ ተቀባይነት እንዳይኖራቸው ለማድረግ የሚሰሩ፣ ከበስተጀርባ እየወጓቸው ያሉ፣ ከአቶ ኃይለማሪያም ሳይሆን ከሌላ ቦታ መመሪያ የሚቀበሉ ቡድኖች ያሉ ይመስለኛል። ከበስተጀርባ ሆኖ የሚሰራ ሌላ ሁለተኛ መንግስት ማለት ነዉ …
ጠቅላይ ሚኒስትሩ «ሰልፎች መደረግ አለባቸው። ሕገ መንግስቱ የሚፈቅደዉን ማገድ አንችልም»   የሚል መመሪያ ይሰጣሉ። ነገር ግን በጎን የኦህድድ አክራሪዎች ፣ በባሌ/ሮቢ « ሰልፍ ካደረጋችሁ ደም ይፈሳል» የሚለው አይነት  ዛቻ በመስጠት ሰልፉን አስተጓግለዋል። በመቀሌ ሕወሃቶች « መቀሌን እንኳን አንድነት ቅንጅትም አልደፈራትም» በማለት የመቀሌ ሕዝብ ድምጹን እንዳያሰማ አድርገዋል። በአዲስ አበባ እንዲሁም ሌሎች ቦታዎች፣  የተከበሩ ዶር ነጋሶን ጨምሮ በርካታ የአንድነት አባላትን እና ደጋፊዎች ታስረዋል። በዉስጣዊና ሚስጥራዊ አሰራር፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩን  ዉሳኔ የመቀልበስ እንቅስቃሴ ሲደረግ ነዉ እያየን ያለነው።
እንደዚያም ሆኖ፣ የአንድነት ፓርቲም ሆነ ሰላሳ ሶስቶቹ የመብት ጥያቄን ከማንሳት ወደ ኋላ አላሉም። በከባድ ሁኔታም ትልቅ መስዋእትነት እየከፈሉ ሕዝቡን እያደራጁትና እያንቀሳቀሱት ነዉ። መስክረም 19 የአዲስ አበባና አክባቢዋ ሕዝብ ድምጹን እንዲያሰማ ቅስቀሳ እየተደረገ ነዉ።
እንግዲህ ለአዲስ አበባ ሕዝብ  መልእክት አለኝ። ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ፣ የፖለቲካዉን ምህዳር ለመክፈት የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ በመደገፍ፣ የአንድነት ፓርቲ፣ ሰላም፣ ፍቅር፣  ብሄራዊ እርቅ፣ መቻቻል፣ ነጻነትና እኩልነት እንዲሰፍን፣  የዜጎች ሰብአዊ መብት እንዲከበር  የሚያደርገዉን እንቅስቃሰሴ በመቀላቀል፣ ኢሕአዴግ ዉስጥ ያሉ በሙስናና በጥላቻ የተዘፈቁ፣ ለሕዝብ ንቀት ያላቸው፣ ያላቸዉን ስልጣን ተጠቅመዉ ዜጎችን እያሸበሩ ያሉትን በመቃወም፣ መስከረም 19 ቀን ሰልፍ በመዉጣት ድምጽህን አሰማ።
ለኢሕአዴግ አባላትና ደጋፊዎችም መልእክት አለኝ። ጥያቄዉ የስልጣን ጥያቄ አይደለም። የፍትህ እንጂ። ጉዳዩ ኢሕአዴግን የመጥላት አይደለም። ኢሕአዴግንም ያካተተ ብሄራዊ እርቅ የማምጣትና የፍቅር እንጂ።
የአንድነት ፓርቲ ሰልፍ የጠራው ኢሕአዴግን በመቃወም አይደለም። ሰልፉ ጸረ-ኢሕአዴግ ሰልፍ አይደለም። ሰልፉ የፖለቲካ ምህዳሩ እንዲሰፋ፣ ብሄራዊ እርቅ እንዲመጣ፣ የታሰሩ የሕሊና እስረኖች እንዲፈቱ፣ በሽብርተኖች ላይ ሳይሆን በሰላማዊ ዜጎች ላይ ያነጣጠረው የጸረ-ሽብር ሕጉ እንዲሰረዝ አሊያም እንዲሻሻል ፣ የኢኮኖሚ እድገት ጥቂቶችን ብቻ ሳይሆን አብዛኛዉን ሕዝብ ባቀፈ መልኩ እንዲቀጥል..የሚጠይቅ ሰልፍ ነዉ። እነዚህንም ጥያቄዎች አገራችዉን የሚወዱና ልቦና ያላቸው፣ የኢሕአዴግ ደጋፊዎች ይጋሩታል ብዬ አምናለሁ። በመሆኑም የመስክረም 19ኙን ሰልፍ እንዲቀላቀሉ አበረታታለሁ። ይሄ የፖለቲካ ጉዳይ ሳይሆን የአገር ጉዳይ ነዉ። ይሄ ለፓርቲ ታማኝነት የማሳየት ወይንም ያለማሳየት ጉዳይ ሳይሆን አገርን የማዳንና ወደፊት የማስኬድ ጉዳይ ነዉ። ከኢሕአዴግ በፊት ኢትዮጵያ !!!! ከአንድነት ፓርቲ በፊት ኢትዮጵያ !!! ከመኢአድ በፊት ኢትዮጵያ !!!!!
በዉጭ  አገር ላለነዉ ይሄን እላለሁ። ሰሞኑን እንደምንሰማዉ ፣ አንዳንዶች፣ በመላዉ ኢትዮጵያ ሕዝቡ እየተንቀሳቀሰ እያዩ፣ በአዲስ አበባ ሰልፎች እየተደረጉ ባሉበት ወቅት፣ ከየት መጡ ሳይባሉ፣  ትኩረት በማጣታቸው ቀንተዉ ነዉ መሰለኝ፣  «መዳን በኢሳያስ አፈወርቂ ነዉ» እያሉን ነዉ። ከጋንዲ፣ ከማርቲን ሉተር ጊንግ፣ ከነአንሳ ሱንኪ፣ከነጂን ሻርፕ በልጠዉ፣ «ስለሰላማዊ ትግል እኛን አትጠይቁ። ከኛ የበለጠ ስለሰላም ትግል የሚያውቅ የለም። ኢትዮጵያ ዉስጥ ሰላማዊ ትግል አይሰራም » በማለት ሲለፍፉ  እየሰማናቸው ነዉ። መንገዱን ጨርቅ ያርግላቸው እላለሁ።
ነገር ግን ይህ አይነቱ የፖለቲካ መርዝ ፣ ብዙዎችን እየበከለ እንዳለም ታዝቢያለሁ። ይሄን አይነት የጥላቻና የጦረኝነት ፖለቲካን በጭፍን ተቀብልን እያስተጋባን ያለን ጥቂቶች አይደለንም። በዚህ ጉዳይ ላይ ወደፊት ብዙ የምንወያይበት ይሆናል። ለጊዜው ግን በዉጭ አገር ያለኸው ወገኔ፣ ሁሉንም በሚዛን ላይ እንድታስቀምጥ እምክርሃለሁ።
በእዉኑ ተስፋህን በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ መጣል ይሻላል ወይንስ፣ የሚገዛዉን ሕዝብ እያሰቃየና እያረዳ ባለ በአንድ የአበደ መሪ ላይ ?  በእዉኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያን ያህል የማይረባ ሆኖ ነዉን ነጻነትና ዲሞርካሲን ከሻእቢያ መጠበቅ የሚገባዉ ? በእዉኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር አመራር አባላት አድራሻቸው ጠፍቶ (ታስረዉና ተገድለዉ) ፣ በኢትዮጵያዊ ፖለቲካ አመለካከታቸው ከበሬታን ያገኙ እንደ ጄነራል ከማል ገልሺና ጀነራል ሃይሉን ጎንፋን የመሳሰሉ ወገኖች ከአገር እንዳይወጡ ታግተዉና ታስረዉ፣ ያለምንም ችግር በቲራቮሎ አስመራር እየተመላለሱ፣ የኢሳያስ አፈወርቂን ታላቅነት የሚሰብኩንን ሰምተን፣ ፊታችንን ሕዝቡ በአሁኑ ወቅት እያደረገ ካለዉ ወሳኝ ትግል ማዞር ይኖርብናልን ? እነዚህ ወገኖች በረጩትስ መርዝ ተስፋ ቆርጠን የአገር ቤቱን ወሳኝ ትግል ከመርዳት መቆጠብ ይግባናልን ? እንግዲህ አገሩን የሚወድ በዉጭ አገር ያለ ኢትዮጵያ ሁሉ እራሱን ይመርምር እላለሁ።
ከሕዝቡ ጎን ቆመናል የምንል ሁሉ የድርሻችህንን እንወጣ። አዲስ አበባ እየደወልን ሕዝቡ ለሰፍ እንዲወጣ እናበረታታ። የሚሊየንም ድምጽ ለነጻነት የተሰኘዉን ንቅናቄ በገንዘባችን እንርዳ። ከዳር ሆነን፣ ወሬ የምንለቃቅም ተመልካቾች አንሁን። የትግሉ አካል፣ ከሚሊዮኖች አንዱ እንሁን !!!!!!!  እኛ ካልተነሳን ማን ? ዛሬ ካልተነሳን መቼ !!!!

No comments:

Post a Comment