Saturday, September 28, 2013

“ግንቦት ሰባት” የጦር መሳሪያ ድጋፍ ከኤርትራ እንደሚያገኝ ገለፀ( by ማህሌት ፋሲል)


በኢትዮጵያ መንግስት አሸባሪ ተብለው ከተፈረጁት ድርጅቶች አንዱ የሆነው የ“ግንቦት ሰባት” አመራሮች ዶ/ር ብርሀኑ ነጋ እና አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ፤ አሁን ያለውን የኢትዮጵያ መንግስት ከስልጣን ለማውረድ ለሚያደርጉት ሁለገብ ትግል ከኤርትራ መንግስት የጦር መሣሪያ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ሰሞኑን ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ በሰጡት መግለጫ አስታወቁ፡፡ ባለፈው ሰኞ ከሶስት መቶ በላይ ለሚሆኑ ኢትዮጵያውያን በአሜሪካ ቨርጂንያ ግዛት የድርጅታቸውን አቋም የገለፁት የድርጅቱ አመራር አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ፤ ከኤርትራ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቅ ጋር በአካል ተገናኝተው እንደተነጋገሩና ከኤርትራ መንግስት ጥሩ ምላሽ ማግኘታቸውን ጠቁመው የመሳሪያ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ተናግረዋል፡፡ በቅርቡ ወደ ትጥቅ ትግል እንገባለን ያሉት አቶ አንዳርጎቸው ፅጌ፤ በስብሰባው ተሳታፊ ከነበሩ ሰዎች፤ ለምን ኤርትራን እንደመረጡና ሌላ አማራጭ ሀገር እንዳልፈለጉ ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ “በአሁኑ ሰአት ባለው ሁኔታ ከኤርትራ የተሻለ ድጋፍ የሚሰጠን የለም” ሲሉ ምላሽ መስጠታቸውን የአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡ “ግንቦት ሰባት” ከአልቃይዳ፣ አልሸባብ፣ ኦነግና ኦብነግ ጋር አሸባሪ ተብሎ በፓርላማ መፈረጁ የሚታወስ ሲሆን የድርጅቱ መሪዎች በሌሉበት የሞትና የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment