Friday, October 4, 2013

ምክትል ጠ/ሚሩ በአቶ መለስ ዜናዊ አሰራር ላይ የመጀመሪያውን ትችት አቀረቡ

መስከረም ፳፫(ሃያ ሦስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አቶ መለስ በስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት ብዙ ስራዎችን መሸከማቸው አፈጻጸም ላይ ድክመት ማምጣቱን በመገምገም የማሻሻያ እርምጃ መወሰዱን ምክትል ጠ/ሚኒስትርና የኢህአዴግ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ደመቀ መኮንን አስታወቁ፡፡ አቶ ደመቀ ከመንግስታዊው አዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ባደረጉትና ትላንትናና ዛሬ ታትሞ በወጣው ቃለምልልሳቸው ላይ አቶ መለስ ብዙ ስራዎችን መሸከማቸው አንዳንድ ዘርፎችን በሚፈለገው ደረጃ ያለመፈተሸ ችግር እንዳጋጠመ አምነዋል፡፡ “ባለፉት ዓመታት ሥራዎቻችንን ስንገመግም ጠቅላይ ሚኒስትራችን ብዙ ስራ ተሸክመው ይሰሩ በነበረበት ወቅት ዋና ዋና የልማት ስራዎች ላይ በማተኮር አንዳንድ የሚኒስቴር መ/ቤቶችና የልማት መስኮች በሚፈለገው ደረጃ ያለመፈተሽ በዝርዝር ዕቅድ ግምገማና ድጋፍ ያለማድረግ ክፍተቶች እንደነበሩ እንደ ችግር በጋራ ያገኘናቸው ነጥቦች አሉ”፡፡ ብለዋል ምክትል ጠ.ሚኒስትሩ ጋዜጣው ከአቶ መለስ ሕልፈት በኋላ በተካሄደው የስልጣን ሽግሽግ በምክትል ጠ/ሚኒስትር ደረጃ የክላስተር አስተባባሪዎች መሾማቸው በአራቱ ብሔራዊ ድርጅቶች መካከል ያለውን አለመተማመን የሚያሳይና ምክትል ጠ/ሚኒስትርነቱን ስልጣን ለሁሉም ለማዳረስ የተደረገ ነው ስለመባሉ ጥያቄ ቅርቦላቸው ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ “አቶ መለስ ታግሎ የሚያታግል ጠንካራ መሪ ነው፡፡እሱን ማጣት ትልቅ ጉድለት ነው፡፡ጉድለቱን ዝም ተብሎ እዚያና እዚህ በዘመቻ የሚሞላ አይደለም” ሲሉ የተናገሩት አቶ ደመቀ፣ ከአቶ መለስ ህልፈት በኋላ አንድ ሰው በቀጥታ አቶ መለስን ባይተካም የጋራ አሰራርን በማጠናከር የተለያዩ የስራ ክፍፍሎች በማድረግ የጋራ አቅም አጎልብቶ እንዴት የህዳሴውን ጉዞ አጠናክሮ መቀጠል ይቻላል የሚለው በስፋት የተመከረበት ጉዳይ እንደነበር አብራርተዋል፡፡ አያይዘውም በሁለት ምክትል ጠ/ሚኒስትር ደረጃ በመሰየም የተለያዩ ክላስተሮችን እንዲያስተባብሩ ማድረግ ያለመተማመን መገለጫ አይደለም በማለት ወቀሳውን አስተባብለዋል፡፡ እነዚህን ችግሮች በመፍታት ድጋፍ ለማድረግ በምክትል ጠ/ሚኒስትር ደረጃ የክላስተር አደረጃጀት ማስፈለጉን የጠቀሱት አቶ ደመቀ የበለጠ አቅም ለማሳደግ፣የተሟላ የመሸከም ብርታት ለመስጠት ይህ የጋራ አሰራር መተግበሩን አስረድተዋል፡፡

No comments:

Post a Comment