Thursday, January 16, 2014

“ በዲሲ መፀዳጃ ቤት የወለደች ሃበሻ” (እየሩሳሌም አራአያ)

በርካታ ኢትዮጲያዊያን በዲሲና አካባቢዋ አእምሯቸው ተነክቶ፣ ለጎዳና ሕይወት ተጋልጠው…ይታያሉ። “ተከፋፍለው” የተቋቋሙ የኢትዮጲያ ኮሚኒቲዎች አሉ። ሃበሻውን እያገለገሉ ወይስ እየተገለገሉበት?…የሚለውን በሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ። አቶ ዳዊት ግዛው የአንዱ ኮሚኒቲ ዳይሬክተር ናቸው። ወደ ቢሯቸው ጎራ ስል አእምሮው የተነካ ሃበሻ ከደጅ ቆሞ ይለፈልፍ ነበር።… ዳይሬክተሩ እንዲህ አሉ፥ «… ሆምለስ የሚባለው ችግር ሁለት አይነት መልክ አለው። አንደኛው ክሮኒክ ሆምለስ ይባላል። ክሮኒክ ማለት ስር የሰደደ ማለት ነው። ስር የሰደደ ስንል ደግሞ ሲጀመር ኢትዮጵያዊ እራሱን አጋልጦ ሁሉን ነገር ካሟጠጠ በኋላ ነው ጎዳና የሚወጣው። ስለዚህ እነዚያን ሰዎች ለመመለስ አስቸጋሪ እና ከባድ ነው። ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ባብዛኛው የክሮኒክ ችግር ነው። በአብዛኛው ጎዳና የምታዩዋቸው ሰዎች ብዙ ዓመታት ያስቆጠሩ ሲሆኑ ሴቶችም አሉ። እድሜያቸው ከ21 አስከ ስልሳዎቹ የእድሜ ክልል ያሉና በክሮኒክ ዙሪያ ውስጥ ያሉ ናቸው። በዚህ ሆምለስነስ ዙሪያ ሲነሳ በጣም የሚያሳዝነኝ ነገር የሁለት ቀን ልጅ መጠለያ ውስጥ ይመጣል ብሎ የሚያስብ የለም። በአንድ ቤተ ክርስቲያን አንዲት አትዮጵያዊት ወጣት ትኖር ነበር። መፀነሷን ሳታውቅና ለሃኪም ሳትናገር ለዘጠኝ ወር ቆይታ በመፀዳጃ ቤት ውስጥ የወለደችበት ሁኔታ ነበር።ከዚያ ወደ ሆስፒታል ተወሰደች። ለሕፃኑ የሕክምና እርዳታ ከተደረገለት በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሲመልሷት ቤተ ክርስቲያን አልቀበልም ይላል።በወቅቱ ወደእኛ መጠለያ እንድትመጣ ይደረጋል። ገና የተወለደ ሕፃን ይመጣል ብለን ስላልገመትን የሕፃን አልጋ አላዘጋጀንም ነበር። ምክንያቱም የሁለት ቀን ልጅ ወደ መጠለያ አይገባም። ለወጣቷ ሸልተር እንድትገባ አንድ ክፍል አዘጋጀንላት። ኢትዮጵያ በአንድ አልጋ ላይ እናት እና ልጅ አብረው ይተኛሉ። አጋጣሚ እኛ ዘንድ ይዘዋት የመጡት ኬዝ ወርከሮቿ ይከታተሏት ስለነበር እኛ ወጣቷን ከነልጇ በአንድ አልጋ እንዲተኙ ስናደርግ “አይሆንም” አሉ። “ምናልባት እንቅልፍ ተኝታ እያለች ስትገላበጥ ልጇን አፍና ልትገድላት ትችላለች፤ ስለዚህ እዚህ መቀመጥ የለባትም። አስወጥተን ይዘናት እንሄዳለን” አሉ። እኔ በአጋጣሚ የሕፃን መኝታ ለመግዛት ሄጄ ነበር። ክሪብ ገዝቼ ስመለስ ሶሻል ወርከሮቹ ይዘዋት ሄደዋል።ከዚያም ከፍተኛ ችግር ተከሰተ። እናቷ የአእምሮ መታወክ ችግር ስለገጠማት ሕፃኗን እዚህ ለሚኖሩ አያቶቿ ትሰጥ ተብሎ ነበር። እናት፣ አባት፣ ወንድምና እህት እዚህ አሜሪካ ነበሯት። እነርሱ ሕፃኗን ተቀብለው እንዲያሳድጉ ሲጠየቁ “በፍፁም አንቀበልም” አሉ። በተደጋጋሚ እኔ እራሴ ሞክሬያለሁ። ሳናግራቸው “አይሆንም” አሉ። በዚያ ምክንያት ለማደጎ እንድትሰጥ ተደረገ። ልጅቷ የትና በምን ሁኔታ ላይ እንዳለች የሚታወቅ ነገር የለም።ሌላው የሼልተር ጉዳይ ሲሆን በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። አሁን ግን መጠለያ አቁመናል።» ብለዋል። ..ሆኖም በሌሎች መጠለያዎች በርካታ ቁጥር ያለው ኢትዮጵያ እንደሚገኝ አልሸሸጉም። ..አስተያየት ስጡበት…
(በፎቶው ዳይሬክተሩ አቶ ዳዊት..)

No comments:

Post a Comment