Tuesday, January 28, 2014

ለፍቅር ሲል ከፍተኛ መስዋእትነት የከፈለ ታዋቂ አርቲስት

Araya Tesefamaryam
አሜሪካ መኖር ከጀመረ 16 አመት አለፈው። ለፍቅር ሲል ከፍተኛ መስዋእትነት የከፈለ ታዋቂ አርቲስት ነው። እጅግ ለሚያፈቅራት ልጅ አቀንቅኖላታል። ይህ ድምፃዊ፥ አበበ ተካ ነው። “ሰው ጥሩ..” የሚለው የግጥም ድርሰት በህልሙ ነበር የታየው። ፍቅረኛው እታገኝ ሙላው ትባላለች።
አቤ በህልሙ “ፍቅረኛውን ጥቅጥቅ ባለ ጫካ ውስጥ እየሮጠ ሲከተላት..ሲሮጥ…ሳይደርስበት ይቀራል። ከዛም ደክሞት ለምለም ሳር በሆነ ሜዳ ቁጭ ብሎ…”ሰው ጥሩ..” እያለ ያዜማል፤”. ህልሙን ለገጣሚ ሙልጌታ ተስፋዬ (ነፍሰ ሄር) ይነግረዋል። ዘፈኑም ተሰራ። “ምንድነው ቀለበት፣.. እንዳንቺ አላየሁም በዝች ምድር ላይ፣.. አገሯ ወዲያ ማዶ፣..በይ ካልረሳሽኝ-ንገሪኝ..” ዜማዎች ለፍቅረኛው እታገኝ የተደረሱ ናቸው። አበበ ተካ በ1989ዓ.ም “ምርጥ የአመቱ ድምፃዊ” ተብሎ የገንዘብና ወርቅ ሽልማት አግኝቷል።
ብዙ ጊዜ መድረክ ላይ ሲዘፍን እንባው ይፈስ ነበር። ምክንያቱ ደግሞ በመለየት ስቃይ ውስጥ አሻግሮ የእርሱ አይነት እጣ (የመለያየት) የደረሰባቸውን እያሰበ ጭምር ነበር።…አበበ በ1990ዓ.ም ለንደን ይጓዛል። በዛው የጣሊያን ፓስፖርት አሰርቶ ፍቅረኛውን ለማግኘት ወደ አሜሪካ ይበራል። እንዳቀደው ግን አልሆነም። ፓስፖርቱ ተመሳስሎ የተዘጋጀ ስለነበረ በአሜሪካ ፖሊስ ተይዞ እስር ቤት ተላከ። 5 አመት ተፈረደበት። ጎንደር ይኖሩ የነበሩት አባቱ አቶ ተካ የልጃቸውን መታሰር እንደሰሙ (በደም ግፊት) ደንግጠው ሕይወታቸው አለፈ። እስር ቤት እንዳለ መርዶ መጣበት።..
አቤ በእስር ቤት በነበረው መልካም ባህርይ 1አመት ከ8 ወር ከታሰረ በኋላ እንዲለቀቅ ተደረገ። በብዙ ፈተና ያለፈበትን ፍቅረኛውን የማግኘት ህልም እውን ሆነ። አበበ አሁን ድረስ ፈጣሪን ያመሰግናል። ከፍቅረኛው እታገኝ ሙላው ጋር ጎጆ ቀልሰው ሶስት ልጆች አፍርተዋል። ልጆቹ ትእግስት አበበ፣ ብርሃን አበበ፣ አዲስኪዳን አበበ ይባላሉ። አበበ እጅግ ሲበዛ ትሁትና ሰው አክባሪ ሲሆን በዲሲ የሚኖሩ ሃበሾች ትልቅ ከበሬታ ይሰጡታል። ስለእርሱ ሲናገሩ፥ « አበበ የትዳርና ፍቅር ተምሳሌት ነው። ጨዋና ቤተሰቡን አክባሪ ሰው ነው። ብዙ ቦታ ልታይ- ልታይ አይልም። ከስራው መልስ ከቤተሰቡ ጋር ነው የሚያሳልፈው። ስለ ሃገሩ ኢትዮጲያ በየመድረኩ ያዜማል።» በማለት ምስክርነት ይሰጣሉ። በየሳምንቱ ቅዳሜ በ”ዱከም” መዝናኛ የሚዘፍነው አበበ ሲናገር፥ « የሰው ልጅ በተለይ በስደት አገር ያለው ሃበሻ ወገኔ..ከሚወደው አገሩ፣ከቤተሰቡ፣ ከፍቅረኛው…እንዲገናኝ ሁሌም ፈጣሪን እለምናለሁ።
የተለያየ ሰው ናፍቆቱን ሳይወጣ ክፉ አይንካው!! ተነጣጥሎ መኖር ከባድ ስቃይ ነው። የናፍቆትና ብቸኝነት ስቃይን የደረሰበት ያውቀዋል። » ይላል። ከኳስ የቡና ክለብ አድናቂና ደጋፊ የሆነው ድምፃዊ አበበ ሁለተኛ አልበም ሊያወጣ ነው። በአንድ ሰው አገናኝነት ገጣሚና ደራሲ Fasil Tekalign የላካቸውን ጨምሮ የግጥምና ዜማ ስራዎች ቅድመ ዝግጅት እየተደረገባቸው ነው። በእውነተኛ ታሪክ ዙሪያ የተመሰረቱ እንዲሁም አገርና ህዝብን የተመለከቱ ዜማዎች ይገኙበታል።..የሰው ልጅ ህልሙ ሲሰምር እንዴት ያስደስታል!!
( አበበና ፍቅረኛው እታገኝ (ከፎቶ ማህደር) ..እንዲሁም በቅርብ ተገናኝተን..)
Source: Ecadforum

No comments:

Post a Comment