Monday, January 13, 2014

በዓሉን ስናከብር የተቸገሩትን በመርዳት ፤ የታረዙትን በማልበስ ፤ የታመሙትን በመጎብኘት ይሁን… ሼህ ኪያር መሃመድ አማን


አዲስ አበባ ፣ ጥር 3 ፣ 2006(ኤፍ.ቢ.ሲ.)በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ የነብዩ መሀመድ መውሊድ በዓል የፊታችን ሰኞ እንደሚከበር ተገለጸ።
በዓሉ በሀገሪቱ በሚገኙ መስጊዶች የሚከበር ሲሆን በዋነኛነት በአዲስ አበባ አንዋር መስጊድ በሀይማኖታዊ ስነ ስርዓቶች እንደሚከበር ፤ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሼህ ኪያር መሃመድ አማን ገልጸዋል።
ፕሬዝዳንቱ የነብዩ መሃመድ መውሊድ በዓልን በተመለከተ ለእምነቱ ተከታዮች የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።
ህዝበ ሙስሊሙ ይሀን በዓል እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ነብዩ ያስተማሩትን እውነት መናገር ፤ ይቅርታ ማድረግ ፤ እንግዳ መቀበልና መፈቃቀርን ሊያሳይ ይገባል ብለዋል።
በበዓሉም  ከመቸውም ጊዜ በላቀ መልኩ የተቸገሩትን በመርዳት ፤ የታረዙትን በማልበስ ፤ የታመሙትን በመጎብኘት ሃይማኖታዊ ግዴታውን መወጣት እንዳለበትም አሳስበዋል።
መላው የኢትዮጵያ ሙስሊም ወገኖች ይህን በዓል ሲያከብሩ ከውጭ የመጡ ወገኖችን በመርዳት ሊሆን እንደሚገባም  ጥሪ አቅርበዋል።
ምክር ቤቱ በቅርቡ ከሳውዲ የተመለሱ ኢትዮጵያውያንን ለማቋቋምና ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመግታት በሚያስችል ስራ እየተሳተፈ ሲሆን ለዚህም 1 ሚሊየን ብር መድቦ ከዘጠኙ ክልሎችና ከሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች የተውጣጣ ብሄራዊ ካውንስል እንዲመሰረት አድርጓል ብለዋል። 
via:http://freedom4ethiopian.blogspot.no

No comments:

Post a Comment