Friday, January 24, 2014

ለወራት ተቋርጦ የነበረው የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ተቃውሞ ተጀመረ

ጥር ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በዛሬው የሰደቃ እና ዱአ መርሀ ግብር በተለያዩ የአገሪቱ ክፍል በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የሚገኙ ሙስሊሞች በእስር ላይ የሚገኙ የመፍትሄ አፈላላጊ የኮሚቴ አባላትን አስበው ውለዋል። እጆቻቸውን ወደ ላይ በማንሳትም ለፈጣሪያቸው ተመጽኖ አቅርበዋል።
በአዲስ አበባ በታላቁ አንዋር መስጊድ በመቶሺዎች የሚቆጠር ህዝብ ተገኝቶ ድዋ አድርጓል። መንግስት የሙስሊሙን እንቅስቃሴ ተቆጣጥሬዋለሁ በማለት መግለጫዎችን ሲሰጥ ቆይቷል። የተለያዩ ፊልሞችን በመስራትም የሙስሊሙን ተቃውሞ ከሽብርተንነት ጋር ለማያያዝ ሙከራ እያደረገ ነው። የዛሬው ተቃውሞ በመንግስት ሊመቀርበው የቅስቀሳ ፊልሞችና በ ቃሊቲ የሚገኙት አስተባባሪዎች ሙስሊሙ ትግሉን እንዲቀጥል ላቀረቡት ጥሪ የተሰጠ ምላሽ ይመስላል።
በሌላ ዜና ደግሞ ከሙስሊሙ ተቃውሞ ጋር በተያያዘ ለእስር የተዳረገው ጋዜጠኛ የሱፍ ጌታቸው በቂልጦ ማረሚያ ቤት ስቃይ እየደረሰበት ነው።
በቂልንጦ በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ የሱፍ ጌታቸው በዞን 2 ውስጥ በተነሳ ፀብ ምክኒያት ሶላት እንዳይሰግዱ መከልከሉ የታወቀ ሲሆን በሰንሰለት ታስሮም ተደብድቧል። ለጋዜጠኛው ቅርብ የሆኑ ምንጮች እንደገለጹት ድብደባው የተፈጸመበት ለምን ብሎ ጥያቄ ስላነሳ ነው። በክፍሉ ውስጥ በቡድን ለተነሳው ጸብ መንስኤ ነህ በሚል ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶታል። በግልም ሆነ በቡድን የኢሻ የመግሪብ የሱብሂ ሶላት በክፍሉም ውስጥ እንዳይሰግድ እገዳ ተጥሎበታል።

No comments:

Post a Comment