Sunday, August 17, 2014

መሬት ላይ ያለን እዉነት በመሸሽ ለዉጥ ማምጣት አይቻልም፡፡

በርእስ እንደተጠቀሰዉ መሬት ላይ የምናየዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ወያኔ ስልጣን ላይ ከመጣ ከ1983 ጀምሮ የብሄር ጥያቄ ፈንድቷል፤ ይህ የማይካድ እዉነት ነዉ፡፡ ይህንን የፈነዳ እዉነት መሸሽ ወይም ያለመስማት መፈለግ የብሄርን ጥያቄ ለሚያነሱ ቡድኖችም ሆነ የፖለቲካ ድርጅቶች የሚደርስባቸዉ ትችት እና መገለል ቀላል አይደለም፤ መተቸቱም፤ ማግለሉም ወይም ማጣጣሉ መፍትሄ አይሆንም ይልቁንም መዉጣት ወደማንችለዉ ችግር ዉስጥ ይከተናል፡፡
ኢትዮጵያ እንደ ሀገር አንድትቀጥል ወይ እንድትቆም ከተፈለገ የብሄር ጥያቄን መመለሱ የግድ ነዉ፡፡ ማድበስበሱ ማለባበሱ ከዚህ ችግር እንድንወጣ አያደርገንም፡፡ እንደዉም ይህንን ጥያቄ በመመለስ ዘለቄታ ያለዉ ሰላም አንድነት እና  ህብረትን ማጠናከር ይቻላል፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ የብዙ ብሄረሰቦች ሀገር፤ ብዙ ቋንቋ እና ባህል ያላቸዉ ህዝቦች የሚኖርባት ሀገር፤ ከልዩንት ይልቅ ብዙ የሚያስተሳስሩን የጋራ የሆኑ እሴቶች ያሉን ህዝቦች ነን፡፡ ስለዚህም ጥቂቱን ጥያቄ በመመለስ ብዙ የሆኑ የጋራ ነገሮቻችንን በማዳበር አንድ ላይ ኢትዮጵያን መገንባት እንችላለን፡፡
አሁን እንደሚታየዉ ከሆነ የጋራ የሆነ ነገራችንን ለማክበር በሚል የተናጠል የሆነዉን መብት መርገጥ ዉጤቱ አሉታዊ መሆኑ የማይቀር ነዉ፡፡ ከላይ እንደጠቀስኩት የብሄር ጥያቄ ኢትዮጵያ ዉስጥ ፈንድቷል፡፡ ይህንን የፈነዳ እሳት መልስ ማዳፈን አይቻልም፤ የሚቻለዉ እነዚህን የብሄር ወይም የማንነት ጥያቄ በመመለስ ኢትዮጵያዊነት ማፅናት ይቻላል፡፡ ካለሆነ ግን እንደ ምስራቅ አዉሮፓ እነደ ኤዢያ ሀገራት ሶቬትህብረት መፈራረስ በኋላ እንደትንንሽ መንደር መሆን ወይም አፍሪካ ስንመጣ ደግሞ እንደ ጅቡቲ፤ፑንትላንድ፤ኤርትራ አይነት ትንንሽ ሀገር እንዳንሆን ስጋቴ ነዉ፡፡ ምክንያቱም የኦጋዴን፤ የአፋር፤ የኦሮሚያ፤ የሲዳማ፤ የአደሬ፤የጋምቤላ...ወዘተ የብሄር ማንነት ጥያቄ ችግሮች አሉና ነዉ፡፡
እንደኔ ምኞት ቢሆን አይደለም ኢትዮጵያ ምስራቅ አፍሪካም አንድ ብንሆን እመርጣለሁ፡፡ እንደዉም ከዚያም አልፎ አንድ ትልቋን አፍሪካን ብንሆን እመርጣለሁ፡፡ይህ ግን በምኞት ብቻ ሳይሆን በተግባርም በሚገለጥ ማሳያም ነዉ፡፡ለምሳሌ፡- የጋራ የሆኑ ትስስሮች እንዲኖሩ በማድረግ፤ በንግድ፤ የጋራ የሆነ ገንዘብ በማተም፤ የጋራ የሆነ ህብረ-ብሄር ጦር በማደራጀት ...ወዘተ፡፡ ብቻ በዛም ሆነ በዚህ የበለጠ ልንቀራረብ፤ ልንተሳሰር ሊያደርጉን የሚችሉ ነገሮችን በመፍጠር በሰላም አብረን መኖር እንድንችል ማድረግ ዉጤቱ ያማረ ነዉ፡፡
ያለበለዚያ ግን አሁን በቅርብ እዚሁ በዲያስፖራዉ ፖለቲካ እንደሚታየዉ በፓል ቶክ ሩሞች(paltalk rooms) የመከፋፈል፤ የመጠላለፍ፤ አንዱ አንዱን ሊጥል የሚደረገዉ ሩጫ መታዘብ ይቻላል፡፡ መቼም እንደሚታወቀዉ ፓል ቶክ (paltalk) በሁሉ አለም ያሉ ወገኖችን የሚያገናኝና ስለ ሀገሩ፤ ስለወገኑ ግድ የሚለዉን ብሶት ማስተነፈሻ ብቻ ሳይሆን፤ የተለያዩ ገንቢም አፍራሽም ሀሳቦች የሚንሸራሸሩበት እደሆነ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ሩሞች ከመለያየት ቢቻል ሊያስማሙን ከሚችለዉ የጋራ ጠላት በሆነዉ በሀገር ህልውና ላይ ችግር እየፈጠረ ያለዉን የወያኔ መራሽ ስርአት ለመገርሰስ ልዩነትን ወደጎን በመተዉ በጋራ መተባበር ነበረባቸዉ፡፡ ነገርግን እንደሚፈለገዉ ሳይሆን በተቃራኒዉ አንዱ አንዱን ለመጣል መታተር የእለት ስራቸዉ ነዉ፡፡ልዩነቶቻችን በበዙ ቁጥር ለገዢዉ መንግስት ስልጣን ላይ መቆየት፤ በህዝብ ላይ የጭቆና ቀንበሩን ለመጫን ጥሩ አጋጣሚ ነዉ፡፡አሁንም ሳይረፍድ እና የባሰ ችግር ዉስጥ ሳንገባ የጋራ ችግሮቻችንን በጋራ እንፍታ፡፡የተለያዩ የብሄር ጥያቄዎቻችን ይመለሱ፤ በጋራ በመግባባት ኢትዮጵያን መገንባት ይቻላል፡፡ በትልቁ የህዝብ ዉክልና የሌለዉን፤ በጉልበት በመሳሪያ ሀይል እያስፈራራ እና እየገደለ ያለዉን ወያኔን ከስልጣን ማዉረድ የሚቻልበትን መንገድ እናጠናክር የእለቱ መልክቴ ነዉ፡፡
መስፍን ሀብተማርያም ነኝ፡፡
አስተያየት ለመስጠት:- mesfinabt@gmail.com እገኛለሁ፡፡ 

No comments:

Post a Comment