Wednesday, February 5, 2014

አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከስልጣን ተነሳ


Sewenet Bishawኢ.ኤም.ኤፍ – የኢትዮጵያን ብሔራዊ ቡድን ከ30 አመታት በኋላ ለከፍተኛ ደረጃ እንዳደረሰ የሚነገርለት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከነበረበት ሃላፊነት መነሳቱን የስፖርት ፌዴሬሽን አሳውቋል። ይህን አስመልክቶ እስካሁን ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኩል ምንም የተሰማ ነገር የለም። ሆኖም ከጥቂት ቀናት በፊት ስፖርት ፌዴሬሽኑ አድርጎት በነበረው ግምገማ ላይ፤ በኢትዮጵያ ላይ ሊገቡ የቻሉት ግቦችን አስመልክቶ፤ አሰልጣኝ ሰውነት ተጫዋቾቹን በመከላከል፤ “ሃላፊነቱን ሙሉ ለሙሉ የምወስደው እኔ ነኝ” ማለቱ ይታወሳል።
ከተጠቀሱት ግቦች መካከል፤ ተከላካይ ደጉ ደበበ ሜዳው ላይ አዳልጦት ከወደቀ በኋላ የገባውን ግብ አስመልክቶ ሲናገር፤ “ደጉ ደበበ በጨዋታም በሩጫም ተበልጦ ሳይሆን፤ ሜዳው አዳለጠው ሌላኛው ተጫዋች አልፎት ሄደ ግብ ገባብን።” በማለት ይህን እና ሌሎችንም ግቦች በተመለከተ ሙያዊ ትንታኔውን ሰጥቶ ነበር። በዚያም ተባለ በዚህ ግን የዚያኑ ቀን እና ከዚያም በኋላ አሰልጣኝ ሰውነት ሃላፊነቱን እንዲለቅ ግፊት ሲደረግበት ቆይቶ ዛሬ ቦታውን ለቋል። ይህንን በተመለከተ እስካሁን ከአሰልጣኝ ሰውነት የተሰጠ መግለጫ ባይኖርም፤ ሰዎች ግን አስተያየት መስጠታቸውን እንደቀጠሉ ነው።
በአንድ በኩል ያለው ወገን… “ተጫዋቾቹን ለዚህ በማብቃቱ እራሱን ከምንም በላይ እላይ አድርሶ ነበር። የሚሰጡ አስተያየቶችን አይቀበልም። በራሱ መንገድ ብቻ ነው የሚመራው። ስለዚህ የተወሰደው እርምጃ ትክክል ነው።” ይላሉ። በሌላ በኩል ደግሞ ከዚህ ተቃራኒ የሆነ አስተያየት ሰጥተዋል።
ሌላው ወገን… “ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ቡድን ለትልቅ ደረጃ አድርሷል። እያንዳንዱ አሰልጣኝ ቡድኑን የሚያዘጋጅበት የራሱ የሆነ መንገድ አለው። አሰልጣኝ ሰውነት ሙያውን ተምሮ እና በዚሁ የአሰልጣኝነት ሙያ የተመረቀ ኢትዮጵያዊ ነው። ቡድኑን ለዚህ በማብቃቱ ቢኩራራ ወይም ሌሎች ጉዳዩ የማይመለከታቸው ሰዎች የሚሰጡትን አስተያየት አለመቀበሉ አይስደንቅም። በራሱ የሚተማመን ሰው የሚሰጠውን ምላሽ ነው የሰጣቸው።” ይላሉ።
በመጨረሻም ከዚህ በፊት ስናደርግ እንደነበረው የራሳችንን አስተያየት በመስጠት ይህን ዘገባ እናጠናቅቃለን። አሁን የተደረገው ውሳኔ ትክክል መሆን እና አለመሆኑን ለታዛቢዎች እንተዋለን። ነገር ግን “አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ተባረረ” የሚለው ዜና በራሱ የሚፈጥረው አሉታዊ ስሜት አለ። አሰልጣኙ ያበረከተውን መልካም ስራ ከግምት ውስጥ በማስገባት፤ ፌዴሬሽኑ… “አባረርን” ከማለት ይልቅ፤ “በክብር አሰናበትናቸው” ማለት ይችላል። ማለት ብቻም ሳይሆን ማድረግም ይቻል ነበር።
አሰልጣኝ ሰውነት ከቦታው ሲነሳ፤ በምትኩ ቦታውን የሚወስደው ስዩም አባተ ሊሆን እንደሚችል እሙን ነው። ስለሆነም አሰልጣኝ ሰውነት እና አሰልጣኝ ስዩም (ወይም ሌላው ተራካቢ) በተገኙበት “የሃላፊነት ሽግግር ተደረገ” ቢባል፤ የተጫዋቹን፣ የደጋፊውንና የሌላውንም ኢትዮጵያዊ ክብር የሚጠብቅ ይሆን ነበር። አሁንም ቢሆን ርክክቡን በኦፊሴል አድርጎ፤ የቀድሞው አሰልጣኝ ለአዲሱ እንዲያስረክብ ማድረግ ይቻላል። ይህ በሚሆንበት ጊዜ ላለነውም ደስ ይለናል፤ ለመጪውም አዲስ አሰልጣኝ ተስፋ ይሰጠዋል። በዚህ የስልጣኔ ዘመን ይህን ማድረግ ካልቻልን ግን አዲሱም አሰልጣኝ ቢሆን፤ መቼ እንደሚባረር ስለማያውቅ በመሳቀቅ የስራ ዘመኑን ሊገፋ ይችላል። ይህ እንዳይሆን ርክክቡን በሰላም እና በፍቅር አድርጉት። በፍቅር የተጀመረ ነገር በፍቅር ያልቃልና – ይህ ነው የዛሬው የኢ.ኤም.ኤፍ መልዕክት።

No comments:

Post a Comment